🔇Unmute
ድሬደዋ፤ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፡-በዐውደ ርዕዩ የቀረቡ የፈጠራ ውጤቶች ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የተጀመሩ ዘርፈ ብዙ ጥረቶች ማሳያ መሆናቸውንየድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር ገለጹ።
"ሳይንስና ቴክኖሎጂ፤ ለፈጣን አገራዊ ዕድገትና ለውጥ" በሚል መሪ ሃሳብ የተዘጋጀውና በድሬዳዋ 1ኛ እና 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የተሰሩ የቴክኖሎጂ እና የፈጠራ ውጤቶች ዐውደ ርዕይ በድሬዳዋ ተጀምሯል።

ዐውደ ርዕዩን የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር፣ የአስተዳደሩ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ አብዲ ሙክታር፣ የትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሱልጣን አልይ እና ሌሎች አመራሮች ከፍተውታል።
ከንቲባ ከድር በወቅቱ እንዳሉት፤ በዐውደ ርዕዩ የቀረቡ የፈጠራ ውጤቶች ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የተጀመሩ ዘርፈ ብዙ ጥረቶች ማሳያ ናቸው።

በመጀመሪያና 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እየተከናወኑ የሚገኙት የሳይንስና ቴክኖሎጂ ውጤቶችን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገርም አስተዳደሩ ድጋፉን እንደሚያጠናክር ተናግረዋል።
በዐውደ ርዕዩ የቀረቡት የፈጠራና የቴክኖሎጂ ውጤቶች የማህበረሰቡን ችግር የሚፈቱ በመሆናቸው ከቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች ጋር በማስተሳሰር ፈጠራዎቹን ወደ ጥቅም የማሸጋገር ስራ በትኩረት ይከናወናል ብለዋል።
የብልፅግና ጉዞው በፍጥነትና በጥራት የሚሳካው ለቴክኖሎጂ ውጤቶች ልዩ ትኩረት እና ድጋፍ በማድረግ መሆኑንም አንስተዋል።
የአስተዳደሩ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሱልጣን አልይ በበኩላቸው፤ አገራዊ ለውጡን ተከትሎ በድሬዳዋ በሚገኙ የ1ኛ እና 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ለቴክኖሎጂ እና ለሳይንስ ፈጠራዎች ልዩ ትኩረት መሰጠቱን አስረድተዋል።

የአሁኑ የትምህርት ቤቶች የቴክኖሎጂ ፈጠራዎችም የአሰራርና አደረጃጀቶች እንዲሁም የድጋፍ እና ክትትል ውጤቶች ናቸው ብለዋል።
በትምህርት ቤቶቹ የተሰሩት የቴክኖሎጂ ውጤቶች የተማሪዎችን የፈጠራ አቅም የሚያሳዩ በመሆናቸው ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ጠቁመዋል።
የፈጠራ ስራዎቹም የበለጠ ዳብረው ለአምራች ኢንተርፕራይዞች፣ ለኢንዱስትሪዎች እና ለአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ጥቅም እንዲውሉ እንደሚሰራ ተናግረዋል።
ዛሬ በተከፈተው እና ለሶስት ቀናት በሚቆየው ዐውደ ርዕይ ላይ በመስኖ፣ በኤሌክትሪክ፣ በአገልግሎት፣ በህክምና፣ በመማር ማስተማርና ለሌሎች ዘርፎችም የሚያግዙ የፈጠራ ስራዎች ቀርበዋል።
微信扫一扫 立即联系我们