🔇Unmute
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018 ዓ.ም (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በዘንድሮ የመኽር እርሻ ወቅት ከ11 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት እንደሚለማ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ።
የክልሉ ግብርና ቢሮ የሰብል ልማት ዳይሬክተር አቶ ሙስጠፋ ሁሴን ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ በመኽር እርሻው ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በዝግጅት ምዕራፍ ላይ ትኩረት ተደርጎ ወደ ስራ ተገብቷል ብለዋል።
በክልሉ በሚገኙ 21 ዞኖችና 29 ከተሞች የመኽር እርሻው በስፋት እንደሚከናወን ገልጸው፤ ለስራው ስኬታማነት ከአርሶ አደሮች ጋር ሰፊ የንቅናቄ ውይይት መደረጉን ተናግረዋል።
በአሁኑ ወቅትም የመኸር አዝመራ ቀደም ብሎ በሚገባባቸው አካባቢዎች የመሬት ዝግጅት ስራ የተጀመረ ሲሆን ስራውም በሜካናይዜሽን ታግዞ እየተካሄደ ይገኛል ብለዋል።

ምርታማነትን ለማሳደግ ግብርናውን ዘመናዊ የማድረግ ስራ ትኩረት እንደተሰጠው ያስታዋሱት ዳይሬክተሩ በዘንድሮ 50 በመቶ የሚሆነውን የእርሻ ስራ በትራክተር ለማከናወን ታቅዷል ነው ያሉት።
በመኽር እርሻ 11 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት የታቀደ ሲሆን ለመኽሩ 2 ነጥብ 1 ሚሊዮን ኩንታል ምርጥና የተሻሻሉ ምርጥ ዘር ይቀርባል ብለዋል።
ከታቀደው ጠቅላላ መሬት ውስጥ 250 ሺህ ሄክታሩ በከተሞች ስር በሚተዳደሩ የገጠር ቀበሌዎች የሚለማ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል።
ለልማቱ ስኬታማነት አስፈላጊ የሆኑ የግብርና ግብዓቶችን በወቅቱ ለማቅረብ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው 2 ነጥብ 1 ሚሊዮን ኩንታል የተሻሻለ ምርጥ ዘር ይቀርባልም ብለዋል።

ለጠቅላላ የእርሻ ስራው 14 ነጥብ 3 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ለማቅረብ የታቀደ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅት 7 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ማዳበሪያ በክልሉ ደርሷል ነው ያሉት።
ከዚህ ውስጥ 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታሉ ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱን ያነሱ ሲሆን በዘንድሮው ዓመት በክልሉ የአፈር ማዳበሪያ እጥረት እንዳይኖር ርብርብ እየተደረገ መሆኑንም አስረድተዋል።
በክልሉ በቴክኖሎጂ የታገዘ የግብርና ኤክስቴንሽን አገልግሎት፤ መስኖ፣ በልግና መኽር እርሻ በስፋት በመተግበሩ ምርትና ምርታማነት በየጊዜው እያደገ መምጣቱንም ዳይሬክተሩ ገልጸዋል።
微信扫一扫 立即联系我们