🔇Unmute
ደብረ ማርቆስ፤ ግንቦት 4/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ምስራቅ ጎጃም ዞን ለማእድን ዘርፉ የተሰጠው ትኩረት ተኪ ምርቶችን በማምረት የውጭ ምንዛሪን ለማዳን የራሱ የሆነ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን የዞኑ ማእድን ሃብት ልማት መምሪያ አስታወቀ።
የመምሪያው ኃላፊ የሻረግ መልሰው ለኢዜአ እንደገለጹት በሀገር በቀል ኢኮኖሚ ሪፎርም ውስጥ ልዩ ትኩረት ከተሰጣቸው አምስት ዘርፎች መካከል የማእድን ልማት አንዱ ነው።
በመሆኑም በዞኑ ያለውን የግራናይት፣ እብነበረድ፣ ጅብሰም፣ ሲልካ ሳንድ፣ የድንገይ ክሰል፣ ብረት፣ ጥቁር ድንጋይና ሌሎች ማእድናትን በማልማት ለስራ እድል ፈጠራና ኢኮኖሚያዊ እድገት ለማዋል ጥረቶች እየተደረጉ ነው ብለዋል።
በዚህም በበጀት ዓመቱ ከማእድን ሃብት ልማት ከ37 ሚሊየን ብር በላይ የሚያወጡ ተኪ ምርቶችን በማምረት የውጭ ምንዛሬን ለማዳን ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን አስታውቀዋል።
ባለፉት ዘጠኝ ወራትም ከ300 ሺህ ኩንታል በላይ ጅብሰምና የኖራ ድንጋይ በማምረት ከ68 ሚሊየን ብር በላይ የሚሆን ተኪ ምርት ማምረት ከጥፍ በላይ አፈፃፀም ማስመዝገብ መቻሉን አብራርተዋል።
ስራውን ለማሳካትም የድጋፍና ክትትል ስራዎችን ከማጠናከር ባለፈ ባህላዊና በአነስተኛ የማእድን ልማት ስራ ለተሰማሩ ወጣቶች የአመራረት ጥራት ላይ ስልጠና መሰጠቱን ጠቁመዋል።
የዘርፉን አቅም በማጠናከር ከ 2 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የስራ እድል መፍጠር ተችሏል ነው ያሉት።
በዞኑ በማእድን ልማት ዘርፉ ተሰማርተው ኢኮኖሚያዊ አቅማቸውን ማሳደግ ከቻሉ ወጣቶች መካከል የአዋበል ወረዳ ነዋሪ ይግዛው ካሴ፤ በግንባታ ጠጠር ምርት ስራ ላይ በመሰማራት ገቢውን ለማሳደግ እንደቻለ ነው የሚናገረው
የደብረ ኤሊያስ ወረዳ ነዋሪው ወጣት ቢያድለው ምህረት በበኩሉ፤ ለኮንስትራክሽን ዘርፉ የሚሆን ማእድን ማውጣት ስራ በመሰማራት ሃብት ማፍራቱን ነው የሚናገረው።
በዞኑ በከፍተኛ ማእድን ልማት ዘርፍ ከ200 በላይ አልሚዎች ፈቃድ ወስደው ወደ ስራ የገቡ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 14ቱ ወደ ማምረት መሸጋገራቸውን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
微信扫一扫 立即联系我们